
በአፍሪካ የመጀመሪያ የሆነው ሀንዳይ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ሞዴል ለገበያ ቀረበ
ቢዝነስ ፅዮን ታደሰ - ሪፖርተር ጋዜጣ ሚያዝያ 14 ቀን 2018 - April 22, 2026
ማራቶን ሞተር ኢንጂነሪንግ በአፍሪካና በመካከለኛው ምሥራቅ የመጀመሪያ የሆነውን የሀንዳይ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ በተመጣጣኝ ዋጋ ለገበያ ማቅረቡን አስታወቀ፡፡ ማራቶን ሞተር ኢንጂነሪንግ ሚያዚያ 10 ቀን 2018 ዓ.ም. ‹‹ሀንዳይ አዮኒክ ዘጠኝ ፍላግሽፕ›› የተሰኘ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ሞዴል ለዕይታ ያቀረበ ሲሆን፣ ይህም የሀንዳይ የመጨረሻ ሞዴል መሆኑን የኩባንያው መሥራችና ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ መልካሙ አሰፋ ገልጸዋል፡፡
‹‹እስካሁን በመካከለኛው ምሥራቅና በአፍሪካ ይህን ሞዴል በማቅረብ የመጀመሪያዎቹ ነን፤›› ያሉት አቶ መልካሙ፣ አዲሱ ሞዴል ከፊት ለፊቱ 70 ከኋላው 160 በአጠቃላይ 230 የፈረስ ጉልበት ለው መሆኑንና አንድ ጊዜ ቻርጅ ተደርጎ ከ850 ኪሎ ሜትር በላይ ርቀት መጓዝ እንደሚችል አስረድተዋል፡፡ የተሽርካሪው ቁመት ከአምስት ሜትር በላይ መሆኑንና ይህን እስካሁን ካሉት የሀንዳይ ሞዴሎች ረዥምና ግዙፍ እንደሚያደርገው ጠቁመዋል፡፡ ማራቶን ሞተርስ ኢንጂነሪንግ ሁሉንም ተሽከርካሪዎችን እያስመጣ የሚገጣጥመው ከደቡብ ኮሪያ ኩባንያ ሀንዳይ መሆኑን፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ ሀንዳይ የሚያቀርባቸው ተሽከርካሪዎች ባላቸው ከፍተኛ ጥራት የታወቀ ነው ብለዋል፡፡ ማራቶን ሞተርስ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን ለገበያ በማቅረብ ቀዳሚ መሆኑን የገለጹት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፣ ከስድስት ዓመታት በፊት ኩባንያው ያቀረባቸውን የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች በመሰብሰብ የባትሪያቸውን ጤና ፍተሻ መደረጉን፣ የሁሉም ተሽከርካሪዎች የባትሪ ጤናማነት መቶ በመቶ ሆኖ መገኘቱን፣ ለዚህም ለደንበኞች አያያዝ የባትሪው ጥራት ምክንያት መሆኑን
አስረድተዋል፡፡
አዲሱን ሞዴል ተሽከርካሪ በምን ያህል መጠን ገበያ ውስጥ ይገኛል ለሚለውና ዋጋውን በሚመለከት ለቀረበላቸው ጥያቄ፣ ‹‹የእኛ የማምረት አቅም በብዙ አሥር ሺዎች በመሆኑ የአቅርቦት ችግር
የለብንም፤›› በማለት፣ ተሽከርካሪዎቹ የቀረቡበት ዋጋም 20 ሚሊዮን ብር እንደማይደርስ፣ ዋጋው ከተሽከርካሪው ሁኔታ አኳያ ተመጣጣኝ ለመሆኑ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ወደ አገር ውስጥ
ሲገባቡ የሚከፈለው ቀረጥ ዝቅተኛ መሆኑ እንደሚያግዝ ገልጸዋል፡፡

